ሰሙኑን ከሚቀጥለው ሃገራዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ በሚድያ የሚደረገው የተፎካካሪ ፓርቲዎችን ሽኩቻ ከኢትዮጵያ ውጭ ሆኜ በመከታተል ላይ ሰነበትኩ።
የውጭ ሃገር ዜጋ ነኝ ግን ኢትዮጵያንና የዋህ ህዝቧ ባንድ በኩል: በሌላ በኩልም መሬቷንና (ዓመት ሙሉ) ባለማቋረጥ የሚፈሱ ወንዞችዋንና ሓይቆቿዋን በ4ቱም መአዝን ከዳር እስከ ዳር የማየቱንና ተወልጄ እስከ 19 ዓመት የማደግን ዕድል ኣግኝቼባታለሁ፡፡ ምንም እንኳን የዛሬ 40 ዓመት ገደማ ኢትዮጵያን ለቅቄ የሄድኩበት ሁኔታ ቢከሰትም፡፡
የእድል ጉዳይ ሆኖ ግን ኢትዮጵያ ከስግብግብ የመሳፍንት አገዛዝ ወደ ፈላጭ ቆራጭ ወታደራዊ መንግስት ብሎም ተምረናል በሚሉ የኢትዮጵያን ህዝብን በዘርና ብቋንቋ ከፋፍለው ሃይማኖታዊና ባህላዊ ትስስሩን በጣጥሰው ከ80 ዓመት በላይ የገዟትን ኢትዮጵያ ሳይና ወደ ኋላ መለስ ብዬ ትዝታዬን ስፈትሽ “ለምን ይሆን” ይች አገር ለቅኝ ገዥዎች አልመችም ብላ ወራሪዎቿን አባራ ስታበቃ: በመልክአ ምድርዋ በበቀሉ ብራሷ ዜጎች ይህን ያህል የምትሰቃየው ለማለት በቃሁ።
በሃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ሰው ከሰው በዘር ግንዱ ይበላለጣል ተብሎ ዘር እየቆጠሩ በስልጣን ኮረቻ ቁጢጥ ማለትና ህዝቡ ወገቡ እስኪሰበር እያሰገዱ መግዛት የዘመኑ ፋሽን ነበር። ሰው ለፈጣሪው እንጂ እንዴት ለሰው ይሰግዳል ብሏል ፊደል የቆጠረው ምሁር፡ በዚያም ምክንያት የግል ይሁን የመንግስት ሰራተኛና ተማሪው ስርዓቱን ሆ! ብሎ በመውጣት ተቃወመ። ሆኖም ህዝባዊ ኣመጹን የሚመራ ብቃት ያለው ድርጅት ስላልነበረ ፍሬ ቢስ ሆነ። ወደ መጨረሻው ግን በኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርሲቲ የተፈጠሩ የምስራቁን ዓለም መጻህፍት ያነበቡ ኢህአፖና መኢሶን እሚባሉ ፓርቲዎች ብቅ ብቅ ኣሉ። ቁምነገራቸው ግን ሰላማዊ ሰልፍ ከማድረግና በህዝብ ገንዘብ የተሰሩ የህዝብ ተቋማትን ከማውደም በላይ ኣላለፈም። በሌላ በኩል የህዝቡን ተቃውሞ ሊያኮላሽ የነበረው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ብሰሜን ኢትዮጵያ ያሁንዋ ኤርትራ ይካሄድ በነበረው ጦርነት ተሰላችቶ ህዝባዊ ኣመጹን ተቀላቀለ። ህዝባዊ ኣመጹን ለመጥለፍ ከሌላው የህብረተሰብ ክፍል የተሻለ ድርጅታዊ መዋቅር ስለነበረው ወታደራዊ ሃይሉን ተጠቅሞ ህዝባዊ ኣመጹን ማስተባበር ላይ ተጠመደ።
የህዝቡን ቀልብ ለመሳብ ያነገበው መፈክር ሶሻሊዝም፡ ኢትዮጵያ ትቅደም ያለምንም ደም፡ መሬት ለኣራሹ ወዘተ የሚሉ በጊዜው ከነበሩ ኣንገብጋቢ ጥያቄዎች በማንሳት ሸብረብ ማለቱን ቀጠለ። በዚህ ኣላበቃም ያኔ ብቅ ብቅ ብለው የነበሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጋብዞ ኣንድ ኣገር ኣቀፍ ፓርቲ እንመስርት ብሎ ጥሪ ኣቀረበ። ይህን የደርግ ወጥመድ ማወቅ የተሳናቸው ጥሪውን ተቀብለው ደርግ ወደ ተቆጣጠረው የ4 ኪሎ ቤተመንግስት ዘው ብለው ገቡ። ሳይውሉ ሳያድሩ እነዚህ በኢ.ሰ.ፓ.አ.ኮ/ኢ.ሰ.ፓ የታቀፉት ፓርቲዎች ኣንዳቸው በሌላው ላይ የውሸት ሪፓርት ለደርግ ከፍተኛ ባለስልጣናት ሹክ ማለቱን ስራየ ብለው ተያያዙት። ደርግም ኣንዳቸው ብሌላው ይሰጡት ይነበረውን ጥቆማ ተጠቅሞ “የፍየል ወጠጤ ትከሻው ያበጠ ልቡ ያበጠበት” እያለ ድራሻቸውን ኣጠፋ። በዚያን ጊዜ ነበር ኢህአፖ (EPRP) ያለ በቂ ጥናትና ዝግጅት የትጥቅ ትግል ኣካሄዳለሁ ብሎ በትግራይ ዓሲምባ ላይ የመሸገው። በተመሳሳይ መንገድ በትግራይ ተሓህት፡ በኦሮሚያ ምድር ኦነግ የየብሄራቸው መንግስት ለመመስረት የትጥቅ ትግል ጀመሩ። የትግራዩ ተሓህት ገና ከጅምሩ በትግራይ ውስጥ ከኔ በቀር ሌላ ድርጅት መንቀሳቀስ የለበትም በማለት ኢህአፖን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶችን ከትግራይ ኣባረረ። ይህ የተበከለ ኣስተሳሰብ እንደ ወረርሽን በሽታ በሁሉም ኣካባቢ ተዛመተ። የኣማራ፡ የዓፋር፡ የጋምቤላ፡ የኦጋዴን ወዘተ ብለው ኢትዮጵያ እምትባለውን ሃገር ተበጣጥሳ ታሪክ ሆና እንድትቀር ለማድረግ ተሞከረ።
በኤርትራ የነጻነት ትግል ያካሂድ የነበረው ሻዕቢያ ኣዝማሚያቸው ደስ ስላላለው ህብረ-ብሄራዊ ኣንድነትችሁን ጠብቃችሁ ኣንድ ላይ ሆናችሁ ደርግን ብትመክቱና ዓለም ኣቀፍ እውቅና ያላትን ኢትዮጵያ በመንደር ለመሸንሸን ኣትሞክሩ ብሎ ጥሪ ኣቀረበ። ሰሚ ግን ኣላገኘም። በተለይ ወያኔ ሻዕብያ ኣሰልጥኖ ባስታጠቀው መሳርያና ጥይት እየተኮሰ የሻዕብያን ስም ማጥፋት ስራየ ብሎ ተያያዘው። ሻዕብያ ግን ወያኔ በመጣበት መንገድ መመለሱን ትቶ ትኩረቱን እንዴት ደርግን መጣል እንዳለበት ኣደረገ።
ዝርዝሩ ብዙ ነው። ገና ከጅምሩ ተው ተነጣጥላችሁ የኢትዮጵያን ህዝብ ጥቅም ኣታስጠብቁም ሲባሉ ከርመው በስተመጨረሻ ብ1981-82 እ.ኢ.ኣ ኢህኣደግ የሚባል ግንባር ፈጠሩ። በዚህ ስምና ድርጅት በወያኔ የበላይነት ብ1983 እ.ኢ.ኣ ኣዲስ ኣበባ ገቡ። ምን ያህል ድጋፍ? ከየት? መቸና እንዴት ያገኙ ነበር በሌላ ግዜ እመለስበታለሁ። ኣሁን ግን ወደ ተነሳሁበት ወቅታዊ ርእስ ልመለስና በሚድያ ስለ ሰማሁት የቃላት ጦርነት ላካፍላችሁ።
-
ኢህኣደግ በሚመራው መንግስት ውስጥ የለውጥ ሃይል ኢህኣደግንና (ወያኔን) ያረጀ ያፈጀ ኣስተሳሰቡን ኣሸንቀንጥሮ ጥሎ ኣውራና ኣጋር ተብለው ይታወቁ የነበሩትን ብሄር ተኮር ክልላዊ መንግስታትን፡ ብልጽግና ፓርቲ ብሎ ኣንድ ላይ ኣሰባሰበ። ታድያ ለምን ይሆን የለውጥ ሃይሉ ራሱ ወገን ዘመዶቼ ናችሁ ሃገራችንና ህዝባችንን የሚጠቅም ሓሳብ ካላችሁ ኑና ኣንድ ላይ ተቀምጠን እንምከር ብሎ ከየተሸጎጡበት ለቃቅሞ ያመጣቸው በኣንድ ረፋድ 107 ዓይነት ዲሞክራሲ ኣለ ይመስል 107 ፓርቲዎች ምስረታ ላይ የተራወጡት? ሰበቡ ኣደገኛ ነውና እባካችሁ የቆየ ቂም በቀል ይቅር ተባብለን ኣንድ ኣይነት ኣመለካከት ያለን ስብስብ ብለን ወደ ሁለትና ሶስት ፓርቲዎች እንታቀፍ ብሎ ያቀረበውን ጥሪ ችላ የተባላው?
-
ለምን ይሆን እዚህም እዛም ተበታትነው ታይተውና ተሰምተው እማያውቁ ፓርቲዎች የለውጥ ሃይሉ ባመቻችላቸው ነጻ መድረክ ላይ ወጥተው የኣንዱ ከሌላው በማይለይ የቃላት ጋጋታ የስድብ ፓለቲካቸውን መደርደር የመረጡት? ለምንስ ይሆን ሃገር ውስጥ በኢህኣደግ ጥላ ስር ታቅፎ የወያኔን ኣበሳና ዱላ ተቋቁሞ ባለው ኣቅም ሃገሩንና ህዝቡን እያገለገለ ለውጡን መርቶ ማክዶናል(Mc Donald´s) ለቀማ ላይ ተበትነው የነበሩትንና ሃገር ውስጥ ትንፋሹን ደብቆ የነበረውን ፓለቲከኛ ነኝ ባዩን ከየወደቀበት ለቅሞ በሃገሩ ጉዳይ ላይ የኣቅሙን እንዲያበረክት ጥሪ ማቅረቡንና ነጻ መድረክ መክፈቱን እንደ ሃጥያት መቁጠር የተፈለገው።
-
ለምን ይሆን እነዚህ 107 የፓለቲካ ፓርቲዎች ኣንድ ላይ ተሰብስቦው መክረው ወደ ምርጫ መግቢያ ፈተናውን (ቅድመ ሁኔታዎችን) ኣዘጋጅተው ሁሉም ብምርጫ ኮሚሽን ታዛቢነት ወደ ውድድሩ ለምዝገባ ሲመጡ ቁመናችሁ ኣይመጥንም ተብለው ገና ለገና 60ዎቹ ‘F’ ኣምጥተው የተባረሩት? በነገራችን ላይ ያለፉትም ኣንዱ የሌላውን ኮርጆ ያለፈ ይመስል ሁሉም ተመሳሳይ መግለጫ ከመስጠት በዘለለ ኣንዳችውም ኣዲስ ሓሳብና መፍትሔ ይዞ የመጣ ኣልሰማንም። ትሩፋታቸው ስድብ፡ ማን እንደ እኔ ጉራ፡ ለዓመታት የተንሰራፋውን ብልሹ ኣሰራር በኣንድ ጀምበር ጠራርገን ኣዲስቷን ኢትዮጵያ እናመጣለን፡ ለዘመናት የተከፈለውን መስዋእትነትና ዓለም ኣቀፍ ህጎችን ረስተው የባህር በር ጥያቄ እንፈታልሃለን ሲሉ ተሰምተዋል። ይህ 84 ብሄሮችን ያቀፈ 110 ሚልዮን የኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጎቱንና ምኞቱን እናስፈጽማለን ስትሉ ለምን እናንተው ራሳችሁ ወደ ሁለትና ሶስት ፓርቲ መታቀፍ ተሳናችሁ? ብሎ እሚጠይቅ ቢያገኙ በቂ መልስ ያገኙ ይሆን? ኣይመስለኝም። እሚገርመው ኣንዳንዶቹ በብሄር ተደራጅተው ለህብረ ብሄራዊትዋ ኢትዮጵያ እንቆማለን ሲሉ መሰማታቸው ነው።
-
ለምን ይሆን ሁሉም ኣፉን የከፈተ ኣስመሳይ የፖለቲካ ፓርቲ በስልጣን ያለውን መንግስት የህግ የበላይነት ኣላስከበረም ብሎ ሲጮህ እሚሰማው? ወያኔ ሆን ብሎ ኢትዮጵያ ውስጥ የፈጠረውን ልዩነት ከማጥበብ ይልቅ ለማስፋት 107 ፓርቲዎች መስርተው ህዝቡን ወደ 107 ኣቅጣጫ እንዲበተን ማድረጉ የህግ የበላይነት ማስከበሩ ላይ ምን ያህል ከባድና ኣደገኛ ሁኔታ እንደፈጠሩ ማየት ተስኗቸው ይሆን? ይህን ያስተዋለ የለውጥ ኣመራሩ ወደ ስልጣን እንደ መጣ ኣውራና ኣጋር ተብለው ቋንቋንና ብሄርን መሰረት ያደረጉ ክልላዊ መስተዳድሮች በኣንድ የፓለቲካ ድርጅት ጥላ ስር ሲያሰባስብ 107 ፓርቲዎች ደግሞ በብሄርና ለይስሙላ ሃገር ኣቀፍ ፓርቲ ብለው ላይታች ሲሉ ማየት የህዝቡን ኣንድነት ጠብቀው ሰላማዊ ኑሮ ለማስቀጠል ወይስ ባቋራጭ የስልጣን ጥማቸውን ለማርካት? ሌላ እነዚህ የፓለቲካ ፓርቲዎች ማየትና ማወቅ ተስኖኣቸው ሳይሆን ሆን ብለው እሚፈጽሙት ወንጀልም ኣለ። ምክንያቱም በስልጣን ያለው መንግስት ህግን የሚያስከብረው ከወያኔ በተረከበው የመከላከያ ሰራዊት፡ የጸጥታና የደህንነት ኣካላቱ ኣድርጎ መሆኑን ኣይደለምና እነዚህ የፓለቲካ ፓርቲ ኣመራሮች መሃይሙ ገበሬም ጠንቅቆ ያቀዋል። ታድያ እነዚህ የተጠቀሱ ህግ የማስከበር ሓይልና ሓላፊነት ያላቸው ተቋማት በማንና? ለምን? እንዴት ተቀርጸው እስከ ለውጡ ማግስት እንደነበሩ ኣልታይ ብሎኣቸው ይሆን? ወያኔ ከዳር እስከ ዳር የኢህኣደግ ኣባላቱንና ጠቅላላ ህዝቡን በዚህ የጸጥታ መዋቅር ኣድርጎ ተቆጣጥሮ፡ ትንፍሽ ማለት እስኪሳናቸው ጠፍሮ ይዘኣቸው እንደነበር ኣያውቅም? ይህን ለውጥ እዉን ያደረጉት ጥቂት መሰል ኣመለካከት ያላቸው የኢህኣደግ ማእከላይ ኮሚቴ ኣባላት የህዝቡን ድጋፍ ሰንቀው ወያኔን ገፍትረው ሲጥሉትና በወያኔ ይሰነዘር የነበረውን ዱላ ተቋቁመው በጥበብ ፈትለክ ብለው ሲወጡ እነዚህ የፓለቲካ ፓርቲዎች የት ነበሩ? የህዝቡን ችግርና ሰቆቃ ከህዝቡ ጋር ሆነን ተጋፍጠናል ይሉ ይሆን? የለውጥ ኣመራር የህግ ኣስከባሪ ሃይሉን ከፓርቲ ወገንተኝነት ነጻ የሆነ ለኢትዮጵያ ኣንድነት የሚቆም ሰራዊት በማደራጀት ላይ እያለ ወያኔ በስልጣን ዘመኑ የፈጸማቸውን ወንጀል ለመደበቅ በኢትዮጵያ ሰላም ማጣት ከሚጠቀሙ ሃገራት ጋር ሆኖ በ3/4 የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ሰሜን እዝ ላይ የሞት ፍርድ ወስኖ ሲተገብር ማነው ከመደምሰስ የተረፈውን ሃይል ኣሰባስቦ የወያኔን እጅ ኣንዴና ለመጨረሻ የሰበረው?
-
ወያኔ ኣዲስ ኣበባን እርግፍ ኣርጎ ትቶ መቀሌ መወሸቁን እማያውቅ ኢትዮጵያዊ የለም። ታድያ ለምን ይሆን እነዚህ ኣሁን ለኢትዮጵያ ህዝብ ጥቅም ቆመናል እሚሉ የፓለቲካ ፓርቲዎች ወያኔ በራሱ ምርጫ ብሕግ ወደ ስልጣን ያመጣውን መንግስት፡ ብሕገ ወጥ መንገድ ከስልጣን ለማስወገድ ወደ ጠራው የመቀሌ ስብሰባ የተቀላቀሉት? ትላንት ጽንፈኛ፡ ትምክህተኛ፡ ሽብርተኛ ብሎ ፈርጆ መግብያ መውጫ ያሳጣቸው ቡድን፡ በምን ተኣምር ነው ለነሱን እንወክለዋለን ላሉት ህዝብ በጎ ነገር ያመጣል ብለው ያሰቡት? ይህ የክህደት ቡድን በኢህኣደግ ማእከላይ ኮሚቴ በነበሩ ኣባላቱ በሙሉ ድምጽ የመረጠውን መንግስት ዓመት ባልሞላ ግዜ ሲክድና ተንኮል ሲሸርብ ነገም በእኛ ላይ ብለው መገመት ተሳናቸው?
ሌላም ሌላም ብዙ ለምን ይሆን ጥያቄዎች ሊነሱ ወቅታዊ ሆኖ ይሰማኛል። እኔ እሚመስለኝን መልስ ከመስጠት ይልቅ የኢትዮጵያ ህዝብ ላለፉት 80 ዓመታት በከርስ ምድሩ ተፈጥረው ያዋረዱትን ጠንቅቆ ስለሚያውቅና ልምዱም ስላለው መዘርዘሩ ኣስፈላጊ ሆኖ ኣላገኘሁትም።
በመጨረሻ ግን ተወልጄ ላደኩባት ኢትዮጵያ እምመኝላትን ኣንዳንድ በጎ ነገራትን ልበልና ኣስተያየቴን ልቋጭ። ይህ ቋንቋንና ብሄርን መሰረት ያደረገ ክልላዊ መንግስት ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ እንደሚመዝን በወያኔ ዘመነ መንግስት በግልጽ ታይቷል። ይህን ያስተዋለ የለውጥ ኣመራር ሁሉንም ኣውራና ኣጋር ተብለው ተነጣጥለው የነበሩትን በብልጽግና ፓርቲ ጥላ ስር ማሰባሰቡ ይበል የሚያሰኝና ኣንድ እርምጃ ወደ ፊት ስለሆነ ኣደንቃለሁ። ምርጫው በሰላም ተጠናቆ ውህደቱ ከዚህ በላይ ተጠናክሮ አዲስ ኢትዮጵያ በቅርብ ግዜ ለማየት በተስፋ እጠብቃለሁ። የለውጡ ኣመራር ከጎረቤት ሃገራት ጋር የጀመረው መልካም ጉርብትናና ለጋራ ጥቅም በጋራ መስራት ያስገኘው ውጤት በቅርቡ በተጨባጭ ስላየን፡ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እመኛለሁ። ኢትዮጵያ በድንበርዋ ውስጥና ደንበር ዘሎ እሚፈሰው ውሃ ለራሷ በቅቶ የጎረቤት ሃገራትን እያጥለቀለቀ መሆኑን ሁሌም እምንሰማውና እምናየው ነው። ይህን ውሃ በከፊል ለመጠቀም ግን ፍቃድ እምንሰጠው እኛ ነን የሚሉ ድንበር ዘለል ሃገራት ሽንጣቸውን ገትረው ሲሞግቱ ኣስተውለናል። እነዚህ ሃገራት ይህን ለማለት የበቁት ሃገሪቱ በዘር፡ በቋንቋና ስፍር ቁጥር በሌላቸው የፓለቲካ ፓርቲዎች ተካፍላለችና ፍላጎታችንን በቀላሉ በነዚህ እናፈጽማለን ከሚል ኣደገኛ ቅማሬ ተነስተው መሆኑን የኢትዮጵያ ህዝብ መገንዘብ ኣለበት። ምክንያቱም ኦነግ ሸኔንና ወያኔ የፈጸሙት ኣስነዋሪ ድርጊት የቅርብ ግዜ ትዝታ ነውና።