ውድ ኣንባብያን ሰላምና ጤና በያላችሁበት ፡ አርእስቱን ሰምታችሁ ወይ አንብባችሁ እናንተም ተገርማችሁ ሃተታውን በጉጉት እንደምትጠብቁ ቅንጣት ጥርጣሬ የለኝም።
ጉዳዩ እንዲህ ነው፦ ሰሙኑን በራሻና በዩክሬን መካከል በተፈጠረው ውዝግብና አንዱ ሌላውን በሃይል ለማንበርከክ እየተወሰደ ያለውን እርምጃ ተከትሎ፡ ምዕራባዊያኑ እዚህም እዛም እንደ እብድ ውሻ ሲራወጡ ታዝበናል። አንዱን ለማውገዝ ሌላውን ለመደገፍ አቅሙም ብቃቱም የለኝም። እድሜ ልኬን ያየሁትን ለማጋራት እንጂ። በፓለቲካል ሳይንስ ወይም በአለም ኣቀፍ ዲፕሎማሲም እዚህ ግባ የሚባል ሰርቲፊኬት የለኝም።
ባለፉት 100 ዓመታት በ3ኛው ዓለም ህዝቦች መካከል ስፍር ቁጥር የሌለው ጦርነት ተካሂዶ የዚያኑ ያህል ህዝብ አልቋል። ይህ እንዳይቀጥል ተብሎ አንዱ ሃገር በሌላው ሃገር ላይ ያልተፈለገ ጦርነት እንዳይከፍት ዓለም-አቀፍ ሕጎችና ደንቦች ተደንግገዋል። ይህን የሚያስፈጽሙ ዓለም-አቀፋዊና አህጉራዊ ድርጅቶች እንዳሉም ይታወቃል። ታድያ ለምን ይሁን በአፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶርያ፣ ሊብያ፣ የመን፣ በቅርብ ጊዜ ደግሞ በኢትዮጵያ ይካሄድ የነበረውን ጦርነት የምዕራቡ ዓለም በቀጥታ ይሁን በቅጥረኛ ልኡካኑ ሲፈጸም አሁን እየታየ ያለውን ያህል ጩሆትና የቃላት ጋጋታ ያልታየው።
ሩቅ ሳንሄድ ባለፉት 60 ዓመታት የኤርትራ ህዝብ ለነጻነቱ ሲታገልና ታግሎ ያገኛትን ሃገር ባላት የሰው ሃይልና የተፈጥሮ ጸጋ ህዝቧን በሚመቸው መንገድ ልሂድ ስትልና እውነተኛ ነጻነቷን ለማጣጣም ስትሞክር፣ በዘመናዊ መሳሪያዎችና እነሱ በሚቆጣጠሩዋቸው የዜና ኣውታሮች ድምጿን ለማፈን ሌተ ተቀን ሽርጉድ ማለት ከጀመሩ አነሆ ሶስት አስርት ዓመታት ተቆጠሩ። ባለፉት 30 የነጻነት ዓመታት አንዴ ከሱማሌው የግብረ-ሽበራ ሃይል ጋር በማስተሳሰር፣ ሌላ ግዜ ደሞ በሰብዊ መብት ረገጣ እነሱ ራሳቸው ክስ መስርተው፣ እነሱ ራሳቸው መስክረውና ዳኝተው በማእቀብ ላይ ማእቀብ ሲጥሉ ከርመዋል። የተባበሩት መንግስታት አባል ሃገራት ተብለው ግን በ3ኛው ዓለም የተፈረጁት መንግስታትም ከምዕራቡ ዓለም የሚደርስባቸውን በትር ፈርተው ድምጽ ከማሰማት ተቆጠቡ። አይገርማችሁም!
እንቀጥል
በጎረቤት ሃገር ኢትዮጵያ ትዘርቶና በቅሎ የጎበዘው እሾህ አሜኬላ የገዛ ብሔሩንና የሃገሩን ኢትዮጵያ ህዝብ መብትና ጥቅም ጥሶ የምዕራቡን ዓለም ፍላጎትና ጥቅም ለማስጠበቅ፡ በ27 ዓመታት የስልጣን ዘመኑ ሽርጉድ ሲል ቆይቷል። ህዝብን ለተወሰነ ጊዜ ማደናገር ይቻል ይሆናል እንጂ ለዘልኣለም አታሎ ለመኖር ማሰብ እራስን ማታለል ነው። ስለሆነም እ ኣ ኣቆጣጠር በ2018 ሃገር-ወዳድ ኢትዮጵያዊያን ባደረጉት ትግል ወያኔ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከመንበረ ስልጣኑ ተገፍትሮ ተጣለ። ዋልታ ተገን ትሆነኛለች ወደላት ትግራይ ፈርጥጦ ገባ። አሁንም ጥጋቡን መቻል ተስኖት በኢትዮጵያ መካላከያ ሰራዊት ላይ ሌትን ተገን አርጎ ሰራዊቱን ጨፍጭፎ ንብረቱን ዘርፎ ለማንበርከክ ሞከረ። ወደ ኤርትራም ሚሳይል ወረውረ፡ ግን ምኞቱ ኣልተሳካለትም።
ከ27 ዓመት በላይ የወሰደው እቅድና ዝግጅት በ15 ቀን ፍርክሽክሹ ወጣ። እቅዱን ያወጡና የመሩ የመንደር ጎረምሶቹ ደግሞ ግማሾቹ ወደ ማይመለሱበት ዓለም ሲጓዙ ግማሾቹ ደግሞ በምርኮ ላይ ይገኛሉ። ታድያ ለምን ይሆን የምዕራቡ ዓለም በአንድ መንደር በበቀሉ ጉረምሶች የአንዲትን ልኡላዊና የUN ቀዋሚ አባል ሃገርን የመከላከያ ሰራዊት የመደምሰስ ሙከራ ሲደረግ እያዩና እየሰሙ ከመንግስት ጎን ቆመው ሕገ ወጡን ስብስብ ከማውገዝ ይልቅ፣ የሽበር ቡድኖችን ሲደግፉና ኢትዮጵያን ብሎም ኤርትራን አለ በተባለ የመገናኛ ብዙሃናቸው ሲወቅሱና ሲያጥላሉ የተሰሙት? በመንግስት ባለስልጣናት ላይ ማእቀብ መጣልስ ምን አመጣው?
ምዕራባዊያን አሁን በዩክሬን ህዝብ ላይ ለደረሰው ሽግር መፍትሄ ለማግኘት ላይ ታች ሲሉ ይታያሉ። ታድያ ለምን ይሆን ትላንት እነሱ ባቀጣጠሉት ጦርነት ከሱርያ፡ ኢራቅ፡ ሊብያ፡ ወዘተ ወደ ስደት ያመራ የነበረውን ህዝብ አይተው እንዳላዮ ዝምታን የመረጡት? ይህን ድርጊታቸው እኛ የ3ኛው ዓለም ህዝቦች ማስተዋልና መተንተን ያቅተናል ብለው ስለሚገምቱ ይሆን? ትላንት ከአማራና ኣፋር ክልል በወያኔ ሰበብ የተፈናቀለው ህዝብ መፈናቀሉ ረገብ እንዲል ሳይሆን መፈናቀሉ እንዲባብስና ሽብር አንዲስፋፋ ደብረሲና ድረስ የሄደውን የወያኔ ጀሌ ሲያበረታቱ ታዝበናል። ይባስ ብለው በህዝብ ተመርጡ ኣዲስ ኣበባ የነበረውን መንግስት እንዲሸሽ፡ ኤምባሲዎቻቸውንና በነሱ የቀጥታ ትእዛዝ ስር የሚተዳደሩ ሃገራት ኤምባሲዎችን ኣገሪቱን ጥለው እንዲወጡ ትእዛዝ ኣስተላልፈዋል።
ጅቡቲ የሚገኝ የኣሜሪካ የጦር አበጋዝ ኣስፈላጊ ከሆነ አዲስ አበባ እንገባለን በማለት ለማስፈራራትም ሞከረ። ምዕራባዊያኑ ተከራይተው ከያዙት የወደብ መሬት ተስፈንጥረው ሉኡላዊት ሃገር ለመውረር ሲቃጣቸው ሩስያ ከመሬቷዋ ተነስታ ባጎራባች ሃገር የተጋረጠባትን ስጋት ለመጋፈጥ ብትሞክር፣ እንዴት ተብሎ ነው የነሱ የቅዱስ ወረራ፣ የራሻውያኑ የዳብሎስ ለመባል የበቃው?
በነገራችን ላይ ይህን አሁን በዩክሬን ህጻናትና በሽማግሌ የእድሜ ባለጸጎች ላይ እየደረሰ ያለውን መፈናቀል ትላንት በሶርያ፣ ኢራቅ፣ ሊብያ፣ ኢትዮጵያ ወዘት ላይ ይደርስ ከነበረው መፈናቀል ለይቸ አላየውም። ምክንያቱም ልብ ስብሩ፣ ደም ያስለቅሳልና።
ውድ ኣንባብያንና ልብ በሉ፣ የዚህ ሁሉ ገፈጥ ቀማሽ ሆነን እስከ መቸ ነው እምንዘልቀው? ትላልቅ ዝሆኖች እርስ በርስ ሲናቆሩና፣ የሃገራቸውን ጥቅም ለማስጠበቅና የስልጣን ዘመናቸውን ለማራዘም ሲራወጡ እኛ ለእድገት ለልማት እምንራወጥ ህዝቡች ነጻነታችን ስማዊ ሆኖ ተረጋግጠን እምንጠብቀው እስከ መቼ ነው? አፍሪካዊያን ስም እየቀያየርን ብሄራዊ ይሆን ሃገራዊ ፓርቲ ተከፋፍለን እርስ በርሳችን ስንወነጃጀል ለነዚህ ስስታሞች በር ከፍተን ኑ ግቡ ርገጡን፣ መዝብሩን ብለን አረንጓዴ መብራት እንዳበራንላቸው ነው እሚቆጠረው።
በሺዎች ኪሎሜተር ተጉዘን የነሱን ስንዴና ንብረት ከመሸመት የልቅ፣ ተፈጥሮ የለገስልንን መሬት፣ ውሃ፣ ጸጋና ጉልበት ተጠቅመን ወደ ልማት በማተኮር ያለንን ለሌላው ጎረቤት ሃገር በማካፈል በጋራ ጥቅም ላይ የተመረኮሰ ገበያ ከፍተን ተጋግዘን ብንሄድ ይመረጣል። ካልሆነ ግን ሰውን ለመርዳት ሳይሆን ለማጥፋት በፈጠሩት የጦር መሳርያ እርስ በርሳችን በመገዳደል፣ ሚስኪኑ ህዝባችንን ጦም እያሳደርን ጦር መሳርያ ግዢ ስንራወጥ ለነሱ ምቹ የጦር መሳርያ ገበያ ሆነን እንቀጥላለን።
በተለይ ኣፍሪካዊያን ውስጣዊ ችግሮቻችን በክብ ጠረጴዛ ተወያይተን መፍታት እየቻልን እስከ መቼ ነው ፈርጣማ ክንድ ወደ ኣላቸው ምዕራባዊያን ጎንበስ ቀና ስንል ጊዜያችንን እምናጠፋ። በኣህጉራችን ሰላም ከሰፈነና እነሱ ወደ አህጉራችን ውስጣዊ ጉዳይ የሚገቡበትን ቀዳዳ ካሳጣናቸው በ100ሺ ቢሊየን ዱላር የተገነባው የመሳርያ ኢንዱስትሪያቸው አፉን ከፍቶ ይቀራል። ይህ እንዳይሆን ነው በአሸበረቁ የዲሞክራሲና፣ ሰብኣዊ መብት ወዘተ ቃላት እያደናገሩ ከኛ በላይ ስለእኛ ተቆርቋሪ መስለው በመታየት ለዘመናት የቆዩት፣ ለወደ ፊትም እሚያቋምቱት። ስለዚህ ይብቃችሁ “#NoMore” እምንልበት ጊዜ ኣሁን ነው።
ለዛሬ እዚሁ ይብቃኝ በቅርብ ጊዜ ስለ ድራጊስቱ ጌታቸው ረዳና ሃሳቡን መግለጽ ስለማይችለው ባለ ፎርጅድ ዶክትሬት ድግሪው ደብረጽዮን ያሰባሰብኩትን መረጃ ይዤ እመለሳለሁ ።
ከ #NoMore ጋር ወደ ፊት!